ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ በተደረገው 4848 የላብራቶሪ ምርመራ ሶስት መቶ ዘጠና ዘጠኝ (399) ሰዎች የኮሮና ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ በሀገራችን ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር 4469 ደርሷል። ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው ሰዎች 195 ወንድ እና 204 ሴት ሲሆኑ የዕድሜ ክልላቸው ከ 4 እስከ 85 ዓመት ውስጥ ይገኛል። በዜግነት 398 ሰዎች ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ 1 የውጭ ሀገር ዜጋ ነው። ቫይረሱ በምርመራ የተገኘባቸው 135 ሰዎች ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ለይቶ ማቆያ፣ 132 ሰዎች ከደዎሌና ጋሊሌ ለይቶ ማቆያ፣ 86 ሰዎች ከአዲስ አበባ 18 ሰዎች ከአማራ ክልል፣ 14 ሰዎች ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፣ 9 ሰዎች ከኦሮሚያ ክልል፣ 2 ሰዎች ከትግራይ ክልል፣ 1 ሰው ከደ/ብ/ብ/ሕ ክልል፣ 1 ሰው ከጋምቤላ ክልል እና 1 ሰው ከሶማሊ ክልል ናቸው።
ከጠቅላላው የላብራቶሪ ምርምራ ውስጥ 22 (8 ከጤና ተቋም እና 14 ከማህበረሰብ በተወሰደ ናሙና) ናሙናዎች በአስክሬን ላይ የተደረገ የላብራቶሪ ምርምራ ሲሆን የኮሮና ቫይረስ የተገኘበት ናሙና የለም።
በቅርቡ የዴክሳሜታዞን (Dexamethasone) መድኃኒት ኦክሲጅን ወይም የመተንፈሻ መሳሪያ እገዛ በሚያስፈልጋቸው የኮቪድ-19 ህሙማን ዘንድ ሊከሰት የሚችለውን የሞት አደጋ መቀነስ እንዳስቻለ መገለጹ ይታወሳል። ይህንንም ተከትሎ የጤና ሚኒስቴር በሀገራችን ኦክሲጅን ወይም የመተንፈሻ መሳሪያ እገዛ ለሚያስፈልጋቸው የኮቪድ-19 ህሙማን የህክምና ባለሙያዎች በሚያዙት መሰረት ዴክሳሜታዞን እንደ ድንገተኛ ህክምና ጥቅም ላይ እንዲውል ወስኗል ።
ነገር ግን ዴክሳሜታዞን የኮቪድ-19 መድኃኒት ያለሆንና ለመከላከል የማይጠቅም ሲሆን የራሱ የሆነ የጎንዮሽ ጉዳት እንዳለው ግንዛቤ እንዲወሰድ እና ያልታመሙ ሰዎች ያለ ህክምና ባለሙያ ትዕዛዝ ከወሰዱት ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን መሆኑ ሊታወቅ ይገባል። ሕብረተሰቡ ያለ ሀኪም ትዕዛዝ መድኃኒቱን እንዳይወስድ እንዲሁም የፋርማሲ እና ሌሎች የጤና ባለሙያዎችም የዴክሳሜታዞን መድኃኒትን ያለ ሐኪም ትዕዛዝ ለደንበኞቻቸው መሸጥ እንደሌለባቸው በአጽንኦት እናሳስባለን፡፡
በሌላ መልኩ በትላንትናው ዕለት ዘጠና አምስት (95) ሰዎች (82 ከአዲስ አበባ፣ 8 ከአማራ ክልል፣ 2 ከሶማሊ ክልል ፣ 1 ከትግራይ ክልል፣ 1 ከኦሮሚያ ክልል እና 1 ሰው ከጋምቤላ ክልል) ያገገሙ ሲሆን በአጠቃላይ በሀገራችን ከበሽታው ያገገሙ ሰዎች ቁጥር 1122 ነው።
በሀገራችን የኮሮና ቫይረስ የሁኔታ መግለጫ
አጠቃላይ የተከናወነ የላብራቶሪ ምርመራ | 211871 |
በሃያ አራት ሰዓት ውስጥ የተከናወነ የላብራቶሪ ምርመራ | 4848 |
በዛሬው ዕለት በበሸታ መያዛቸው በላብራቶሪ የተረጋገጠ | 399 |
በአሁኑ ሰዓት ቫይረሱ ያለባቸው | 3273 |
በፀና የታመሙ ሰዎች ቁጥር | 30 |
አዲስ ያገገሙ | 95 |
በአጠቃላይ ያገገሙ | 1122 |
በዕለቱ ከኮሮና ቫይረስ ጋር በተገናኘ ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች | 0 |
በአጠቃላይ በበሽታው ሕይወታቸው ያለፈ | 72 |
ወደ ሀገራቸው የተመለሱ | 2 |
እስከ አሁን ድረስ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር | 4469 |
የላብራቶሪ ምርመራ ናሙናዎች ከተለያዩ ይበልጥ ተጋላጭ ከሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎች፣ ከጤና ተቋማት፣ በቫይረሱ ከተያዘ ሰው ጋር የቅርብ ንክኪ ካላቸው ሰዎች እንዲሁም በአስገዳጅ ለይቶ ማቆያ ውስጥ ካሉ ሰዎች ተወስዶ የተከናወነ ነው፡፡
በማንኛውም ሰዓት ጥቆማ ለመስጠትና መረጃ ለማግኘት እንዲሁም በቫይረሱ መያዛቸው ከተረጋገጡ ሰዎች ጋር የቅርብ ንክኪ ያላቸው ግለሰቦች ሪፖርት ለማድረግ በነፃ የስልክ መስመር 8335 ወይም በ952 ወይም በመደበኛ የስልክ ቁጥር 0118276796 በመደወል ወይም በኢሜል አድራሻችን ephieoc@gmail.com በመጠቀም ወይም ባሉበት ክልል በተዘጋጁ ነፃ የስልክ መስመሮች በመደወል ሪፖርት እንዲያደርጉ ወይም በአካባቢው ለሚገኙ ጤና ተቋማት በስልክ እንዲያሳውቁ እንጠይቀለን፡፡
ዶ/ር ሊያ ታደሰ
የጤና ሚኒስትር
ሰኔ 13 ቀን 2012 ዓ.ም